በረከት ፀጋዬ
ምድብ አምስት
አልጄሪያ፣ ሴራሊዮን፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ አይቮሪኮስት
አልጄሪያ
- ተሳትፎ: 19ኛ ጊዜ
- ምርጥ ውጤት፡ ሻምፒዮን (1990፣2019)
- አሰልጣኝ፡ ጀማል ቤልማዲ
- ኮከብ ተጫዋች፡ ሪያድ ማህሬዝ

ምን ይጠብቃሉ፡ አልጄሪያ የአፍሪካ ዋንጫ ክብራቸውን ለማስጠበቅ ብቻ ወደ ካሜሮን አልመጡም። በተከታታይ ጨዋታ ያለ መሸነፍ ክብረ ወሰንን ማሻሻል ዕቅዳቸው ይሆናል። ጣልያን 37 ጨዋታዎችን ባለመሸነፍ ሪከርዱን በአውሮፓ ዋንጫው ጨብጠዋል። የበረሃ ቀበሮዎቹ ኮሎምቢያ፣ቱኒዝያ፣ ሴኔጋል፣ ናይጄሪያ እና ሜክሲኮን የመሳሰሉ ቡድኖችን ሳይቀር ሰይፋቸውን በማሳረፍ (በማሸነፍ) ይህን ሪከርድ በቅርበት እያዩት ይገኛሉ።
ከኮከባቸው ሪያድ ማህሬዝ ግቦችንና ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን መስጠት በእጅጉ ይጠብቃሉ። ሌላው ያልተዘመረለት ኮከብ እና አብዶኛ ዩሱፍ ብላይሊ በቡድኑ ውስጥ ይገኛል። ይህ የ30 አመት ተጫዋች በተለይም ከልጅነት አንስቶ ከማህሬዝ ጋር ያለው ጥሩ ኬሚስትሪ ለቡድኑ ተጨማሪ የማጥቃት ሃይል ይሆነዋል። አሰልጣኝ ጀማል ቤልማዲ ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል መልኩ ከሁለት አመት በፊት ዋንጫውን ሲያነሱ የተጠቀሙበትን ቋሚ 11 አሁንም እንደሚመርጡ ይጠበቃል።
ከሁለት አመት በፊት የ4-3-3 አሰላለፍን በስፋት ሲጠቀሙ የተስተዋሉት ቤልማዲ በማጣሪያ ጨዋታዎች ወቅት 4-4-2 ዳይመንድን መጠቀማቸው ተቀያያሪ ታክቲክን ለመጠቀም እንደሚያስቡ ይጠቁማል። በብዙ መስፈርቶች በተለይም ጥራት ባለው የቡድን ውህደት አልጄሪያ አሁንም ለዋንጫው ከፍተኛ ተገማች ነች። በቅርብ ያሸነፉት የአረብ ካፕ ለዳግም ድል ተቀዳሚ እጩ እንዲሆኑ አስተዋጽኦ ያበረክታል።
ሴራሊዮን
- ተሳትፎ: 3ኛ ጊዜ
- ምርጥ ውጤት፡ ምድብ ማጣሪያ (1994፣96)
- አሰልጣኝ፡ ጆን ኬስተር
- ኮከብ ተጫዋች፡ ኪ ካማራ
ምን ይጠብቃሉ፡ ሴራሊዮን ከ26 አመታት በኃላ ወደ አህጉሪቱ ትልቅ የውድድር መድረክ መመለስ ችለዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ ከምድብ ማለፍን ያልማሉ። ይህን ለማሳካት ግን በምርጥ አቋማቸው ላይ መገኘትን አጥብቀው ይሻሉ። ከባዱ ሃላፊነት በእጃቸው የወደቀው ጆን ኬስተር ቡድኑን በአዳዲስ ተጫዋቾች በማዋቀር ሶስተኛውን ተሳትፎዋቸውን ለመጀመር ተዘጋጅተዋል። የሊዮን ኮከቦቹ ሙሉ ተስፋቸው በአንጋፋው አጥቂ ኪ ካማራ ላይ ያርፋል።

የአምስት ጊዜ የአሜሪካ ሜጀር ሶከር ሊግ ኮከብ አግቢው ካማራ ቡድኑ ወደ ካሜሩን ቲኬት እንዲቆርጥ ያስቻለች ወሳኝ ግብን ቤኒን ላይ በፍፁም ቅጣት ምት ማስቆጠሩ ይታወሳል። ከአልጄሪያና አይቮሪኮስት ልቀው የምድብ ማጣሪያውን ለማለፍ ሴራሊዮናውያን ከባድ ፈተና እንደሚጠብቃቸው መተንበይ ቀላል ይመስላል።
ኢኳቶሪያል ጊኒ
- ተሳትፎ: 3ኛ ጊዜ
- ምርጥ ውጤት፡ ግማሽ ፍፃሜ (2015)
- አሰልጣኝ፡ ሁዋን ሚቻ
- ኮከብ ተጫዋች፡ ኤምልዮ ንስዌ
ምን ይጠብቃሉ፡ ይህ ስም ያለፉትን ጥቂት አመታት የአፍሪካ እግር ኳስ ለተመለከተ አዲስ አይደለም። ካለፉት 9 አመታት አፍሪካ ዋንጫዎች ሁለቱ በዚህች የነዳጅ ሃብት ባላት ሃገር የተሰናዱ ነበሩ። ይህ የአፍሪካ ዋንጫ ከሃገራቸው አፈር ውጪ የሚያደርጉት የመጀመሪያ የአፍሪካ ዋንጫ ነው። ተጫዋቾቻቸው በትላልቅ የአውሮፓ ክለቦች ባይጫወቱም አብረው ለረጅም ጊዜ መቆየት የቻሉ ናቸው ሲል ቢቢሲ ያትታል።

የቡድኑ ምርጥ ተጫዋች ፔድሮ ኦብያንግ በጉዳት ከቡድኑ ስብስብ ውጪ ሆኗል። በስፔን እና ጣልያን ሁለተኛ ዲቪዝዮን የሚጫወቱ እንደ ጆሴ ማቺን፣ ኢባን ሳልባዶር የመሳሰሉ ቁልፍ ተጫዋቾች በአሰልጣኙ የቡድን ስብስብ ውስጥ ይገኛሉ። በዚህ ሲዝን ክለብ አልባ የሆነውና የቀድሞ ማዮርካ፣ ሚድልስብራ፣ በርሚንግሃም ሲቲ አጥቂ ኤሚሊያኖ ንስዌ የቡድኑ አሞበልና ሌላው ቁልፉ ተጫዋች ነው።
የቡድኑ የመከላከል ድክመት በዚህ ውድድር አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳይፈጥር ያሰጋል። ያለፉትን አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች ያልተሸነፉት እና በዓለም ዋንጫው ማጣሪያ ቱኒዝያን 1-0 ቢረቱም በመጨረሻ አንደኝነቱን ባሸነፏት ሃገር የተቀሙት ‘ነጎድጓዶቹ’ ለሁለቱ የምድቡ ሃያላን ሃገራት ፈተና መሆናቸው የሚቀር አይመስልም።
ኮትዲቯር
- ተሳትፎ: 24ኛ ጊዜ
- ምርጥ ውጤት፡ ሻምፒዮን (1992፣2015)
- አሰልጣኝ፡ ፖትሪስ ቢያሜሌ
- ኮከብ ተጫዋች፡ ፍራንክ ኬሲዬ
ምን ይጠብቃሉ፡ ዝሆኖቹ ከአለም ዋንጫው ማጣሪያ የመጨረሻ ምዕራፍ የቀሩበትን አሳፋሪ ጉዞን ተከትሎ ቡድኑን የመልሶ ግንባታ ውስጥ የከተተው ይመስላል። እንደ ሰርጂ ኦሪዬ፣ ኤሪክ ባዬ፣ ማክስ ግሬድልና ሴሪ ዲዬን የመሳሰሉ ተጫዋቾቻቸው በእግር ኳስ ህይወታቸው ወደ መጨረሻው ምዕራፍ የደረሱ እንደመሆናቸው ቡድኑ ሁለተኛ እቅድ እንዲኖረው ያስገድደዋል።
እንደ ዊልፍሬድ ዛሃ፣ ሰባስትያን ሄለር እና ማክስዌል ኮርኔት የመሳሰሉ ተጨዋቾች ቡድኑን ቢቀላቀሉም የኋልዮሽ ጉዞውን ሊቀለብስ አልቻለም። የአፍሪካ ዋንጫውን ያሸንፋሉ? ምላሾች ሁለት መልክ ያላቸው ናቸው። ደካማ ተከላካይ፣ የግብ ዕድል መፍጠር አለመቻል፣ በእነ ዲዲዬ ድርግባ ጊዜ የነበረው አይነት የሚያነሳሳ የቡድን መሪ አለመኖር ዝሆኖቹን ለዋንጫው እንዳይታጩ ያደርጋቸዋል።

በሌላ ጎን አሰልጣኙ በአዲስ የቡድን ግንባታ ሂደት ላይ እንደመሆናቸው እና አሁንም ከዋክብት በቡድኑ ውስጥ መገኘታቸው አይቮሪያውያኑ ሙሉ በሙሉ ተስፋ እንዳይቆርጡ ያደርጋቸዋል። ሆኖም ከፊታቸው ብዙ ተግዳሮቶች መኖራቸው እሙን ነው። በተለይ፣ በተለይ መልበሻ ቤቱን መቆጣጠር ለፖትሪስ ቢያሜሌ ትልቁ የቤት ስራ ነው።
ከወርቃማው ትውልድ መልስ ይህን ምድብ ከአልጄሪያ በላይ ሆኖ ለመጨረስ ዝሆኖቹ ከፊት የሚጠብቃቸው ትልቅ ፈተና ይሆናል። ይህን ፈተና ለመወጣት ከማንቸስተር ዩናይትዱ ኤሪክ ባዬ፣ በርንሌዩ ማክስዌል ኮርኔ፣ ኤስ ሚላኑ ፍራንክ ኬሲዬ፣ የፓላሱ ዊልፊ ዛሃ፣ የአርሰናሉ ኒኮላ ፔፔና የዚህ ሲዝን የአውሮፓ ቻምፒዮንስ ሊግ ኮከብ ግብ አስቀጣሪ የአያክሱ ሰባስትያን ሄለር ደጋፊው ብዙ ይጠብቃል።
የጨዋታ መርሃ ግብር
ማክሰኞ ጥር 3/2014
አልጄሪያ vs ሴራሊዮን (ቀን 10:00 ሰዓት)
ረቡዕ ጥር 4/2014
ኢኳቶሪያል ጊኒ vs አይቮሪኮስት (ምሽት 4፡00 ሰዓት)
እሁድ ጥር 8/2014
አይቮሪኮስት vs ሴራሊዮን (ምሽት 1፡00 ሰዓት)
አልጄሪያ vs ኢኳቶሪያል ጊኒ (ምሽት 4፡00 ሰዓት)
ሐሙስ ጥር 12/2014
አልጄሪያ vs አይቮሪኮስት (ምሽት 4፡00 ሰዓት)
ሴራሊዮን vs ኢኳቶሪያል ጊኒ (ምሽት 4፡00 ሰዓት)
ምንጮች፡
- ጎል አፍሪካ ድህረ ገፅ www.goalafrica.com
- ዩሮስፖርት ድህረ ገፅ www.eurosport.com/AfricanCupOfNations
- BBC ስፖርት www.bbc.com