
አርሴናል ወደ ኪንግ ፓወር ስቴድየም ተጉዞ ሌስተር ሲቲን በማሸነፍ በዋንጫው ፉክክር መሪነቱን ያስቀጠለበት ሦስት ነጥብ ማግኘት ችሏል።
ሁለተኛው አጋማሽ ጅማሬ ላይ በማርቲኔሊ ብቸኛ ጎል ጨዋታውን ማሸነፍ የቻሉት መድፈኞቹ በጨዋታው ከወትሮው ለየት ያለ አቀራረብ ይዘው ቀርበዋል። ይህም በፊት መስመር አጥቂነት ትሮሳርድ መሰለፉ ነው። በእንቅስቃሴም ተጨዋቹ ሃሰተኛ ዘጠኝ ቁጥር ሚናን ሲተገብር ተስተውሏል።
ሃሰተኛ ዘጠኝ ቁጥር ሚና እግርኳስ ቅርፅ እና ወግ ይዞ መካሄድ ከጀመረ ወዲህ በርካቶች የተለያየ ጊዜ ላይ መተግበር እንደተጀመረ ያስረዳሉ። ያም ሆነ ይህ ሃሰተኛ ዘጠኝ ቁጥር ሚናን ሊዮኔል ሜሲን በመጠቀም የፔፕ ግዋርድዮላን ያህል የተገበረ አለመኖሩ ያስማማል።
ሃሰተኛ ዘጠኝ ቁጥር ሚና ትርጉሙ እንደወረደ፤ አጥቂ(9 ቁጥር) ተጨዋች ሊገኝ ከሚገባው ቦታ ውጪ አብዛኛውን የጨዋታ ጊዜ ሲያሳልፍ ነው። ይህም በተጠና አካሄድ የተጋጣሚን ተከላካይ(የ9 ቁጥሩን ማርከር) ቦታውን አስለቅቆ በሌሎች ተጨዋቾች ይተለቀቅውን ‘ስፔስ’ ማጥቃት ነው።
ሌስተር ሲቲዎች ለአርሴናል ለወጥ ያለ አቀራረብ የሰጡት ምላሽ ትኩረትን የሚስብ ነበር። የጨዋታውን አብዛኛው ክፍለጊዜም በፋያስ የሚመራው የተከላካይ ክፍል የትሮሳርድን እንቅስቃሴ መቆጣጠር ችሏል።
እንዴት?
የሌስተር ሲቲ መኅል ተከላካይ እና መሪ ፋዬስ በትሮሳርድ ከመሳብ ይልቅ የኋላ 4 ተጨዋቾችን(እራሱን ጨምሮ) መስመር ጠብቆ ይገኝ ነበር። ትሮሳርድን በሳጥን ውስጥ የፋዬስ ሃላፊነት ሲሆን ተጨዋቹ በጥልቀት ሲመለስ ደግሞ የተከላካይ አማካዩ ንዲዲ ሃላፊነቱን ይረከባል።
በምስሉ ላይ እንደሚታየው፣ ትሮሳርድ በጥልቀት ተመልሶ ኳስ ሲቀበል ንዲዲ ይጫነዋል።

የተለቀቀ ክፍተት ባለመኖሩ የአርሴናል መስመር አትቂዎች ሩጫዎችን ማድረግ አይችሉም። ትሮሳርድ ያለው አማራጭ ኳሱን ወደ መስመር ለሳካ ማውጣት ነው።

ሳካ በነፃነት መስመር ላይ ኳስ ቢያገኝም ከክሮስ ውጪ አማራጭ ያለው አይመስልም::

ወደ መስመር የወጣውን ኳስ ከሳካ ተቀብሎ ኋይት ቢያሻግርም፣ በቁጥር ሳጥን ውስጥ የነበሩት የሌስተር ሲቲ ተከላካዮች ትሮሳርድን ጨምሮ ኳሱን ለመግጨት የተገኙትን የአርሴናል ተጨዋቾች እድል አልሰጡም።

በሌላ አጋጣሚም በትሮሳርድ እንቅስቃሴ የተሳበው ፋዬስ በእጅ ምልክት ከንዲዲ ጋር ሲነጋገር ይታያል።’የአንተ ሃላፊነት ነው የሚል ምልክት’

ወድያውም ንዲዲ ወደ ትሮሳርድ፣ ፋዬስም ወደ ኋላ መስመሩ…

የመጀመርያውን አጋማሽ ከሞላ ጎደል የአርሴናልን የማጥቂያ ቀጠና እንቅስቃሴ መገደብ የቻሉት ሌስተሮች በሁለተኛው አጋማሽ መጀመርያ ደቂቃዎች ባሳዩት መዘናጋት ዋጋ ከፍለዋል።
ከግብ ጠባቂ መስርተው ለመውጣት በሚሞክሩበት ሰዓት የቀኝ ተከላካዩ ካስታኜ ሁለተኛው የሜዳ ክፍል ላይ ይገኛል።

ካስታኜ በሁለተኛው የሜዳ ክፍል ኳስን ተቀብሎ ለመጫወት ቢሞክርም የአርሴናል ካውንተር ፕሬስ ፋታ የሚሰጥ አልነበረም። ጋብሬል ማጋሌሽ ለማፅዳት የሞከረውም ኳስ በዕድል በሚመስል መልኩ የካስታኜን የተከፈተ ቀጠና ላይ የነበረው ትሮሳርድ አገኘ።

የአርሴናል የማጥቃት ሽግግር ከመጀመርያው አጋማሽ በተቃራኒ ቅርፁን ላጣው የሌስተር ኋላ መስመር ለመቋቋም ከባድ ነበር። ማርቲኔሊ ጎሉን ለማስቆጠር ያደረገው የሽምጠጣ ሩጫ እና የተረጋጋ አጨራረስ አስገራሚ ነበር።

ከዚህ ጨዋታ ሌስተር ሲቲ ምንም ናገር ይዘው መውጣት ባይችሉም፣ ብጨዋታውም የማጥቃት እንቅስቃሴያቸው እምብዛም ባይሆን፤ ለአርሴናል የሃሰተኛ ዘጠኝ ቁጥር የአጨዋወት ስልት አስተማሪ የሆነ ምላሽን ሰጥተዋል።