
በረከት ፀጋዬ
ምድብ ስድስት
ቱኒዝያ፣ ማሊ፣ ሞሪታንያ፣ ጋምቢያ
ቱኒዝያ
● ተሳትፎ፡ 20ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት፡ ሻምፒዮን (2004)
● አሰልጣኝ፡ ሞንድሄር ኬባይር
● ኮከብ ተጨዋች፡ ሃኒባል መጅብሪ

ምን ይጠብቃሉ፡ የአለም ዋንጫ ማጣሪያዎችን እና በቅርብ በካታር ተካሂዶ ፍፃሜውን ባገኘው የአረብ ካፕ ላይ የካርቴጅ ንስሮቹን ብቃት ለተመለከተ በአፍሪካ ዋንጫው ቀላል ተፎካካሪ እንደማይሆኑ ያስባል። አሰልጣኙ ሞንድሄር ኬባይር በአጨዋወታቸውና አጥጋቢ ውጤት አላመጡም በሚል ተደጋጋሚ ትችትን ከደጋፊዎች ያስተናግዳሉ።
በተለይ አሰልጣኙ የሚመርጧቸው ተጨዋቾች እና የአጨዋወት ዘይቤ ብዙ ጊዜ መከላከልን ያበዛሉ በማለት ደጋፊዎች ይተቻሉ። ይህ የመከላከል አጨዋወት ዘይቤ ግን እንደ ተጋጣሚዎቻቸው ሲቀያየር ይስተዋላል። የኤስፐራንስ ደ ቱኒስ ተጨዋች የሆነው ሞሃመድ አሊ ቤን ሮምዳኔ ሊታዩ ከሚገባቸው ተጫዋቾች አንዱ ነው። የማንቸስተር ዩናይትዱ ሃኒባል መጅብሪ እና አንጋፋው አጥቂ ዋሂብ ካዝሪ ቱኒዛውያን የሚመኩባቸው ሌሎች የቡድኑ ኮከቦች ናቸው።
ቱኒዝያ ብዙ ጊዜ ባለቀ ደቂቃ ውጤትን በመቀየር ወደ ቀጣዩ ዙር እያለፉ ደጋፊዎቻቸውን ‘ሰርፕራይዝ’ ያደርጋሉ። ወጣ ገባ የሚለው አቋማቸው እንዳለ ሆኖ የካርቴጅ ንስሮቹ አሁንም ለዋንጫው ከሚታጩት ብሄራዊ ቡድኖች ተርታ ይመደባሉ።
ማሊ
● ተሳትፎ፡ 12ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት፡ የፍፃሜ ተፋላሚ (1972)
● አሰልጣኝ፡ ሞሃመድ ማጋሱባ
● ኮከብ ተጫዋች፡ ሙሳ ጄኔፕዮ
ምን ይጠብቃሉ፡ ንስሮቹ ወቅታዊ አቋማቸው መልካም የሚባል ነው። በአለም ዋንጫው ማጣሪያ ምንም ሳይሸነፉ እና ግብ ሳይቆጠርባቸው የክታር ትኬት ለመቁረጥ 180 ደቂቃ ብቻ ይቀራቸዋል። ማሊ በካሜሮን ምድር መጫወት ገድ አላቸው ይሏቸዋል፦ 1972 ፍፃሜ የደረሱበት እንዲሁም አምና የተካሄደው ቻን አፍሪካ ዋንጫ የፍፃሜ ተፋላሚ የነበሩት በዚሁ ተመሳሳይ ቦታ ነበር። የንስሮቹ ደጋፊዎች በቡድናቸው ስብስብ፣ ብስለትና ወቅታዊ አቋም ይተማመናሉ።
ከአመታት በፊት በተለያዩ የወጣቶች ውድድር መድመቅ የቻለውየማሊ ቡድን የያኔው ታዳጊዎች አብዛኞቹ አሁን በብ/ቡድን ደረጃ በመጫወት ላይ ይገኛሉ። ከ2015 እስከ 2017 ድረስ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ሻምፒዮን፣ የአለም ከ20 ዓመት በታች ውድድር የብር ሜዳሊያ ባለቤት የነበሩት አብዛኞቹ ተጫዋቾች በዚ ስብስብ ውስጥ ይገኛሉ። ተንታኞች ይህን ለቡድኑ እንደ ጥንካሬ ማሳያ አድርገው ያነሱታል።

ማሊያውያን በዚ አፍሪካ ዋንጫ ሁለት ትልቅ ዕድሎችን በእጃቸው ይዘዋል። በአለም ዋንጫው ማጣሪያ የቡድኑ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ የሆነውና በኖርዌይ ሊግ የሚጫወተው ኢብራሂማ ኮኔ በቡድኑ ውስጥ መገኘትና ከ2017 አንስቶ ማጋሱባ በአሰልጣኝ መንበሩ ላይ መገኘት (የተረጋጋ አሰልጣኝ መያዛቸው) ለቡድኑ ትልቅ መነሳሳትን ይፈጥራል። ማሊ በካሜሮን ሳይጠበቁ ረጅም ርቀትን ሊጓዙ ከማችሉ ብ/ቡድኖች በግንባር ቀደምትነት ይጠራሉ።
ሞሪታንያ
● ተሳትፎ፡ 2ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት፡ ምድብ ማጣሪያ (2019)
● አሰልጣኝ፡ ዲዲዬ ጎሜዝ ዲ ሮሳ
● ኮከብ ተጫዋች፡ አቡበከር ካማራ
ምን ይጠብቃሉ፡ በህዳር ወር ቡድኑን የተረከቡት የቀድሞ የኢት ቡና አሰልጣኝ ዲዲዬ ጎሜዝ በአረብ ካፕ በተወሰነ ረገድ ፈተናቸውን ጀምረዋል። ቡድኑን የማስተካከል ሃላፊነት የተጣለባቸው ጎሜዝ አለወሳኝ ተጫዋቾቻቸው በአረብ ካፕ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴን ማሳየት ችለዋል። በአውሮፖ የተለያዩ ሊጎች የሚጫወቱት አቡበከር ካማራ፣ ኢብራሂማ ኩሊባሊ፣ አሊ አቤድን የመሳሰሉ ተጫዋቾቻቸውን ሲያገኙ ቡድኑ የበለጠ እንደሚጠናከር ይጠበቃል።

ቴክኒካል አማካሪዎች ቡድኑ የበለጠ ተጠቃሚ የሚሆንበትን መንገድ በመለየት እና ተጫዋቾችን በመመልመል አሰልጣኙን ሲረዱ መቆየታቸውን ቢቢሲ አስነብቧል። ‘ሞራቢቶንስ’ በምድቡ አብረዋቸው ያሉትን ሃገሮች በሚገባ ያውቋቸዋል። ከሁለት አመት በፊት በግብፅ አፍሪካ ዋንጫ ያሸነፈቻቸው ማሊና ባላንጣቸው ቱኒዝያን የሚገጥሙ ይሆናል።
መክፈቻ ጨዋታቸውን ከጋምቢያ ጋር ማድረጋቸው በብዙ ይረዳቸዋል። ሽንፈትን ማስወገድ ከቻሉ ለቀጣይ ጨዋታዎች በብዙ ጠቀሜታው የጎላ ነው። ከምድቡ የማለፍ ፈተና ለሞሪታንያ ከባድ ይመስላል። ሆኖም የውድድሩን እንግዳዋ ሃገር ጋምቢያን ማሸነፍ ከቻሉ ጥሩ ሶስተኛ ሆኖ ማለፍን እንዲያስቡ ሊያደርጋቸው ይችላል።
ጋምቢያ
● ተሳትፎ፡ ለመጀመሪያ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት: –
● አሰልጣኝ፡ ቶም ሴይንትፌት
● ኮከብ ተጫዋች፡ አሳን ሲሴ
ምን ይጠብቃሉ፡ በአፍሪካ ዋንጫው ከሚካፈሉት ሁለት እንግዳ ሃገሮች አንዷ ጋምቢያ በማጣሪያው ዲሞክራቲክ ኮንጎ ያለችበትን ምድብ አንደኛ ሆና ማለፏ በአስገራሚነቱ ይታወሳል። ትንሿ የምዕራብ አፍሪካ ሃገር ጋምቢያ 2018 ላይ ቶም ሴይንትፌትን ከሾሙ በኃላ መሻሻላቸውን ሚዲያዎች ዘግበዋል። ለአምስት አመታት ያህል ምንም ጨዋታ ያላሸነፈች ሃገር ቤኒን ያሸነፉት ከእርሳቸው ሹመት ማግስት ነበር። ሆኖም በአጨዋወት መንገዳቸው የቀድሞው ናሚቢያና ቶጎ አሰልጣኝ ሴይንትፌትን የሚተቿቸው አልጠፉም።

ከስድስት ቡድኖች አራቱ ጥሩ ሶስተኛ ሆነው ማለፋቸውና በአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታ የማሸነፍ ታሪክ ከሌላት ሞሪታንያ ጋር የመጀመሪያ ጨዋታ ማድረጋቸው ማለፍ እንደሚችሉ እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል። አሳን ሲሴ(ኤፍ ሲ ዙሪክ)፣ ሙሳ ባሮው(ቦሎኛ)፣ ኤብሊ ጃሎው(ሲሪያንግ)፣ ኦማር ኮሊ(ሳምፕዶሪያ)፣ ሰኢዶ ጃንኮ ለእንግዳዋ ጋምቢያ የውድድሩ ረጅም ርቀት መጓዝ ቁልፍ ሚናን ለመጫወት የደጋፊውን አደራ ተቀብለው ካሜሩን ከትመዋል።
የጨዋታ መርሃ ግብሮች
ረቡዕ ጥር 4/2014
ማሊ vs ቱኒዝያ (ቀን 10፡00 ሰዓት)
ሞሪታንያ vs ጋምቢያ (ምሽት 1፡00 ሰዓት)
እሁድ ጥር 8/2014
ጋምቢያ vs ማሊ (ቀን 10፡00 ሰዓት)
ቱኒዝያ vs ሞሪታንያ (ምሽት 1፡ዐዐ ሰዓት)
ሐሙስ ጥር 12/2014
ማሊ vs ሞሪታንያ (ምሽት 4፡ዐዐ ሰዓት)
ቱኒዝያ vs ጋምቢያ (ምሽት 4፡00 ሰዓት)
ምንጮች
● ጎል አፍሪካ ድህረ ገፅ www.goalafrica.com
● ዩሮስፖርት ድህረ ገፅ www.eurosport.com/AfricanCupOfNations
● BBC ስፖርት www.bbc.com