
ጥቅምት 2022 ላይ ባየር ሌቨርኩሰን ቁርጠኛ ውሳኔ ላይ መድረስ ነበረባቸው፡፡ በስዊዘርላንዳዊው አሰልጣኝ ጄራልዶ ሲየዋኔ ስር ውጤታማ ባለመሆናቸው ለመለያየት ወሰኑ፡፡ በወቅቱም ምርጫቸው ያደረጉት ወጣቱን አሰልጣኝ ዣቢ አሎንሶን ነበር፡፡ አሎንሶ በሪያል ሶሲዬዳድ ታዳጊ ቡድን ከሰራው ስራ ውጭ ዋና ቡድንን የመያዝ ልምድ አልነበረውም፡፡ ዳይ ቨርክሰልፍ ግን እምነታቸውን ስፔናዊው ላይ አድርገዋል፡፡

Girmaldo pic via Getty Images
አሎንሶ በተጫዋችነት ዘመኑ በታላላቅ አሰልጣኞች ስር ከመስራቱ ባሻገር በርካታ ዋንጫዎችን አሳክቷል፡፡ ቻምፒዮንስ ሊግ፤ አውሮፓ ዋንጫ እና አለም ዋንጫ ከድሎቹ መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ ከምንም በላይ ግን በባየር ሌቨርኩሰን የሰራው ድንቅ ስራ በታሪክ መዝገብ ላይ ሰፍሯል፡፡ አሎንሶ በመጀመሪያ የአሰልጣኝነት አመቱ ወራጅ ቀጠና ላይ የሚገኙትን ሌቨርኩሰን ስድስተኛ እንዲጨርሱ አስችሏል፡፡ በዩሮፓ ሊግም እስከ ግማሽ ፍጻሜ መጓዝ እንዲችሉ ምክንያት ሆኗል፡፡ በድንቅ አጨዋወት የሚለይ ቡድንም መስርቷል፡፡
በክረምት የዝውውር መስኮት ደግሞ ልምድ ያላቸው ተጫዋቾችን ወደስብስቡ መቀላቀልን መርጧል፡፡ ወጣቶቹን በማፍራት ለሚታወቁት ሌቨርኩሰን ይህ አዲስ ውሳኔ ነው፡፡ ግራኒት ዣካ ከአርሰናል ፤ አሌሳንደሮ ጊርማልዶ ከቤንፊካ እንደዚሁም ዮናስ ሆፍማን ከቦሩሲያ ሞንቼንግላድባህ ተቀላቅለዋል፡፡
ከእነዚህም ተጫዋቾች በተጨማሪ ናይጄሪያዊያኑን ኔታን ቴላ እና ቪክተር ቦኒፌስ ፈርመዋል፡፡ በሁሉም ውድድሮች ያልተሸነፈ ለሶስትዮሽ ዋንጫ የሚፋለም ቡድን መስርተዋል፡፡
እሁድ እለትም ቨርደር ብሬመንን 5 ለ 0 በመርታት የናፈቁትን የቡድንደስሊጋ ዋንጫ አሸንፈዋል፡፡ ድንቁ ወጣት ፍሎሪያን ቨርትዝም ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ደምቋል፡፡ አርሰናልን በመልቀቅ ወደጀርመን የተመለሰው ዣካ የመጀመሪያ የሊግ ድሉን አሳክቷል፡፡ በዚህ ጨዋታም ከርቀት ያስቆጠራት ግብ በባይ አሬና የተገኘውን ታዳሚ ጮቤ አስረግጣለች፡፡
በ120 አመታት ታሪካቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ሌቨርኩሰን የሊጉ አሸናፊ ሆነዋል፡፡ ዣቢ አሎንሶም ደማቅ ታሪክን መጻፍ ችሏል፡፡ የስፖርቲንግ ዳይሬክተሩ እና የቀድሞው የክለቡ ተጫዋች ሲሞን ሮለፍስ በበኩሉ ወሳኝ ሚና መጫወት ችሏል፡፡
ዶርትመንድ በአስገራሚ ሁኔታ ባለፈው የውድድር ዘመን ያጣውን ዋንጫ ሌቨርኩሰን በድንቅ መንገድ አሳክቷል፡፡ በናግልስማን ፊት አውራሪነት እና በሬድ ቡል ድጋፍ ላይፕዚሽ ያላሳኩትን ጀብድ ሌቨርኩሰን እውን አድርገውታል፡፡
የባየርን ሙኒክም የ11 አመታት የአይበገሬነት ጉዞ እዚህ ላይ ተገቷል፡፡ አሁን ኔቨርኩሰን የሚባለው የስላቅ ስም ቀርቷል፡፡ የአሎንሶ ልጆች ደማቅ ታሪክ ጽፈዋል፡፡ የጀርመን እግር ኳስ አድናቂዎች ብቻ ሳይሆኑ መላው አለም የማይረሳው ገድል ተፈጽሟል፡፡
ይህ ቡንደስሊጋ ነው፡፡ ከምንም በላይ የደጋፊዎች ድምጽ የሚጎላበት፡፡ ስቴዲየሞች በህበረ ቀለማት የሚደምቁበት፡፡ የግቦች ፌሽታ የሚስተዋልበት፡፡ ወጣት ተጫዋቾች የሚፈሩበት እናም ታሪክ የሚሰራበት፡፡
ቀጣዩ ጥያቄ ደግሞ ይነሳል፡፡ ሌቨርኩሰን የጀርመን ዋንጫን እና ዩሮፓ ሊግን ያሳካሉ፡፡ ይህንንስ ምንም ጨዋታ ሳይሸነፉ ያደርጉታል; በጊዜ ሂደት የምናየው ይሆናል፡፡