የአፍሪካ ዋንጫ ተሳታፊ ብሄራዊ ቡድኖች አጭር ምልከታ ( ምድብ 1)

በረከት ፀጋዬ

33ተኛው ቶታል ኢነርጂስ አፍሪካ ዋንጫ በካሜሩን አስተናጋጅነት ከጥር 1-29 ይካሄዳል። አስተናጋጇ ሃገር ዋንጫውን በሃገራቸው ለማስቀረት ይፈልጋሉ። ለ33 ጨዋታዎች ያህል ያለመሸነፍ ጉዞ ላይ ያሉትና የወቅቱ የአፍሪካ ሻምፒዮኖች አልጄሪያ ቢያንስ ያለመሸነፍ ጉዞዋቸውን ወደ አምስት ከፍ የማድረግ ፍላጎት አላቸው።

በፊፋ ወርሃዊ ደረጃ የወቅቱ የአህጉሪቱ አንደኛ ሴኔጋል ምንም እንኳን የአፍሪካ ዋንጫውን ለአንድ ጊዜ እንኳ ለመሳም ባይታደሉም ይህን ታሪክ ለመቅረፍ ጊዜው አሁን እንደሆነ ይረዳሉ።

ግብፃውያን ከአለም ምርጥ ተጫዋቾች አንዱን ይዘዋል፤ አፍሪካ ዋንጫን ማሸነፍ ለእነርሱ ትርጉሙ ብዙ ነው። ጋና አፍሪካ ዋንጫን ካሸነፈች ከ40 አመት በላይ ሆኗታል። ይህን ታሪክ ትቀይር ይሆን? ለእርሶ አፍሪካ ዋንጫውን የማሸነፍ ቅድመ ግምት ለማን ይሰጣሉ? ቀጣዩ አጭር ጥንቅር ተሳታፊ ብ/ቡድኖችን በአጭሩ ይዳስሳል። መልካም ንባብ!

ምድብ አንድ
ቡርኪናፋሶ፣ ኬፕ ቨርድ፣ ካሜሮን፣ ኢትዮጰያ

ቡርኪናፋሶ


● ተሳትፎ፡ 12ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት፡ የፍፃሜ ተፋላሚ (2013)
● አሰልጣኝ: ካሙ ማሎ
● ኮከብ ተጫዋች: በርትራንድ ትራኦሬ
● ምን ይጠብቃሉ: ያለፈውን የአፍሪካ ዋንጫ ማለፍ አለመቻላቸው ቁጭትን የፈጠረባቸው ፈረሰኞቹ ይህን ወደ ኃላ ትተው የተሻለ ውድድርን ለማሳለፍ ያቅዳሉ። ወደ ክታሩ አለም ዋንጫ የሚወስዳቸውን ትኬት ለመቁረጥ የመጨረሻው 10 ምርጦች ውስጥ ለመግባት እስከ መጨረሻው አልጄሪያን ቢፈትኑም በጠባብ ውጤት ምድቡን በበላይነት ማጠናቀቅ ሳይችሉ ቢቀሩም እንደ በርትራንድ ትራኦሬ እና አብዱል ታፕሶፓ የመሳሰሉ ከዋክብትን ይዘው ከምድቡ ረጅም ርቀትን መጓዝን ያልማሉ።

ካላቸው ጥራት በተጨማሪ የአዕምሮ ጥንካሬን ለመፍጠር በማሰብ በአመቱ መጀመሪያ የስነ ልቦና ባለሙያ ወደ ቡድኑ መቀላቀላቸው ግባቸውን ለመምታት የበለጠ እንደሚረዳ ታምኖበታል በማለት ቢቢሲ ዘግቧል። ሳይጠበቁ በ2013 የደቡብ አፍሪካው ውድድር እስከ ፍፃሜ ድረስ የተጓዙበትን አቅም አሁንም መድገም እንደሚችሉ ያምናሉ። እሁድ ጥር 1 በመክፈቻው ቡርኪናቤ አስተናጋጇን ካሜሩን በግዙፉ ኦለምቤ ስታዲየም በመግጠም ውድድራቸውን አንድ ብለው ይጀምራሉ።

ቡርኪናፋሶ

ኬፕ ቨርድ
● ተሳትፎ: 3ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት: ሩብ ፍፃሜ (2013)
● አሰልጣኝ: ቡቢስታ
● ኮከብ ተጫዋች: ራያን ሜንዴዝ
● ምን ይጠብቃሉ: ያለፉት አስር አመታት ለትንሿ የባህር ዳርቻ ሃገር እግር ኳስ ትልቅ ለውጥን የፈጠረ ነበር። በመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ በ2013 ሩብ ፍፃሜውን የተቀላቀሉት ሰማያዊ ሻርክስ ፌዴሬሽኑ በተከተለው ትውልደ ኬፕ ቬርድ ተጫዋቾችን ከአውሮፓ በመሰብሰብ ጠንካራ ቡድንን የመስራት ፕሮጀክት በእጅጉ ተጠቅመዋል። ምንም እንኳን ካለፉት 4 ውድድሮች ሁለቱ ላይ መካፈል ባይችሉም ቡድናቸው ጠንካራ መሆኑን በቀረቡባቸው መድረኮች በሚገባ አሳይተውናል።

ከካታር አለም ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ ከናይጄሪያ ሁለት ነጥቦች ርቀው መጨረሳቸው ከግምት ሲገባ ኬፕ ቨርድ በዚህኛው መድረክም ለምድቡ ቀጥተኛ ተፎካካሪዎቻቸው ከባድ የቤት ስራ መሆናቸው አይቀርም። ምንም እንኳን ለመጨረሻ ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫ የተመለክትናቸው 2015 ላይ ቢሆንም እግር ኳሳቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻልን በማሳየቱ ኬፕ ቬርዳውያን ደስተኛ ናቸው። ምድባቸውን በማለፍ እስከ ሩብ ፍፃሜ ድረስ መጓዝን እንደ ትልቅ ውጤት እንደሚያዩት የቀድሞ የቡድኑ አሰልጣኝ ሉሲዮ አንትዮኔስ ለቢቢሲ አስተያየታቸውን ይሰጣሉ። ”ካሜሩን በርግጥም ይህን ምድብ በበላይነት ለመጨረስ የብዙዎች ግምት ናት፤ ሁለተኛ ሆኖ ለማለፍ ፉክክሩ በኛና ቡርኪናፋሶ መሃል ይመስለኛል። ኢትዮጵያ የምድቡ ዝቅተኛ ተገማች ቢሆኑም እናከበራቸዋለን” ሲሉ ተደምጠዋል።

ኬፕ ቨርድ

ካሜሩን

● ተሳትፎ: 20ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት፡ ሻምፒዮን (1984፣88፣ 2000፣02፣17)
● አሰልጣኝ፡ አንቶንዮ ኮንሴንሳኦ
● ኮከብ ተጫዋች: ኤሪክ ማክሲም ቺፖ ሞቲንግ
● ምን ይጠብቃሉ: በሜዳቸው ላይ ውድድሩ እንደ መካሄዱ ከምድቡ ወደ ቀጣይ ዙር ማለፍ ብቻ ሳይሆን እስከ መጨረሻው ተጉዘው ዋንጫውን ሃገራቸው ላይ ማስቀረት በእጅጉ ይፈልጋሉ። ምንም እንኳን እንደ ቀደሙት ጊዜያት የአፍሪካ እግር ኳስ የሃይል ሚዛንነት አብሯቸው ባይሆንም የማይበገሩት አንበሶች በአውሮፓ ሊጎች መድመቅ የቻሉ ከዋክብትን ይዘዋል።

በክረምቱ የሴሪ አውን ክለብ ኢንተር ሚላን ለመቀላቀል ፊርማውን ያኖረው የአያክሱ ግብ ጠባቂ አንድሬ ኦናና፣ በውሰት ከፋልሃም ናፖሊን ተቀላቅሎ ጥሩ የውድድር አመት እያሳለፈ የሚገኘው አንድሬ ፍራንክ ዛምቦ አንጉዊሳ እና የባየር ሙኒኩ አጥቂ ኤሪክ ማክሲም ቺፖ ሞቲንግ ከነዚህ ውስጥ ይጠቀሳሉ። ቡድኑን ከ2019 ወዲህ የተረከቡት ፖርቹጋላዊ አሰልጣኝ ኮንሴንሳኦ እርሳቸው ቡድኑን ከያዙት ወዲህ መሻሻሎችን እንዳሳዩ ይነገራል።

የክንፍ ተጫዋቾችን አቅም አውጥተው በመጠቀም በመከላከልና በማጥቃቱ ረገድ የተመጣጠነ ቡድን እንደገነቡ ተገልጿል። ከሶስት አመት በፊት ከጥሎ ማለፍ የወደቁትና ከአምስት አመት በፊት ዋንጫውን ማሸነፍ የቻሉት ካሜሩናውያን ይህ ለስድስተኛ ጊዜ ዳግም መንገስ የሚችሉበት መድረክ እንደሚሆን ያምናሉ።

ካሜሩን

ኢትዮጵያ

● ተሳትፎ፡ 11ኛ ጊዜ
● ምርጥ ውጤት፡ ሻምፒዮን (1962)
● አሰልጣኝ፡ ውበቱ አባተ
● ኮከብ ተጫዋች፡ ጌታነህ ከበደ
● ምን ይጠብቃሉ፡ የወደቁት አናብስት (the fallen giants) የካፍ፣ አፍሪካ ዋንጫው መስራቾች እና የቀድሞ ሃያል ሃገር ቢሆኑም ከመሰረቱት ውድድር ከሶስት አስርት አመታት በላይ ማለፍ አለመቻላቸውና በ40 አመት ይህ ሁለተኛ ተሳትፏቸው መሆኑ በርግጥም ይህን ስያሜ ያሰጣቸዋል ሲል የዩሮ ስፖርት ዘጋቢው ኢብራሂም ሙስጠፋ ይናገራል።

በአብዛኛው ሃገር በቀል ተጫዋቾችን ያካተተውን ቡድን በውድድሩ ረጅም ርቀት መጓዝ እንደሚከብደው ጠቅሶ በቅርብ የአለም ዋንጫ ማጣሪያዎች ያሳዩት ብቃት በተለይም ከጋና ጋር አቻ መለያየታቸው በአንፃራዊነት ከእነርሱ በበላይነት ለተቀመጡት የምድብ ሃገራት መልዕክቱ ጠንካራ እንደሚሆን ኢብራሂም ሙስጠፋ ይጠቅሳል። መሰረታቸውን አፍሪካ ውስጥ ያደረጉ በርካታ የስፖርት ድህረ ገፆች የቡድኑን ወጣት የፊት አጥቂ አቡበከር ናስር በማድነቅ በውድድሩ መድመቅ ከሚችሉና ሊታዩ ከሚገባቸው ተጫዋቾች ተርታ ያስቀምጡታል። ይህ የወቅቱ የኢትዮጽያ እግር ኳስ ኮከብና የአምናው የሊጉ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ፣ ባለ ሪከርድ ተጫዋች በቅርብ አመታት ከኢት ቡና ወጥቶ በውጪ ሃገራት ክለቦች ሲጫወት ልንመለከተው እንችላለን ሲሉም ግምታቸውን ያስቀምጣሉ። ዋልያዎቹ ከምድብ ካለፉ ከእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ የ9 ሚሊዮን ብር ሽልማት ቃል የተገባላቸው ሲሆን አሰልጣኙ ውበቱ አባተ ቡድኑ ለረጅም ጊዜ አብሮ የቆየ እንደሆነና የማሸነፍ ፍላጎቱ ከፍተኛ መሆኑን በመጥቀስ የ33ኛው አፍሪካ ዋንጫ ሳይጠበቅ ብዙ ርቀት የሚጓዝ (surprising team) እንደሚሆን አምናለው ሲል በቡድኑ የሽኝት ፕሮግራም ወቅት አስተያየቱን ሰጥቷል።

ኢትዮጵያ

የጨዋታ መርሃ ግብሮች

እሁድ ጥር 1/2014
● ካሜሩን vs ቡርኪናፋሶ (ምሽት 2፡00 ሰዓት)
● ኢትዮጵያ vs ኬኘ ቨርድ (ምሽት 4፡00 ሰዓት)

ሐሙስ ጥር 5/2014
● ካሜሩን vs ኢትዮጵያ (ምሽት 1፡00 ሰዓት)
● ቡርኪናፋሶ vs ኬፕ ቨርድ (ምሽት 4፡00 ሰዓት)

ሰኞ ጥር 9/2014
● ቡርኪናፋሶ vs ኢትዮጽያ (ምሽት 1፡00 ሰዓት)
● ኬፕ ቨርድ vs ካሜሩን (ምሽት 1፡00 ሰዓት)

ምንጮች፡
● ጎል አፍሪካ ድህረ ገፅ www.goalafrica.com
● ዩሮስፖርት ድህረ ገፅ www.eurosport.com/AfricanCupOfNations
● BBC ስፖርት www.bbc.com

Girmachew Kebede

Founder of Tilafok.com, Girmachew Kebede is a sports journalist with more than a decade of newsroom and on-air experience. He served as Deputy Editor-in-Chief at Ethio-Sport newspaper, was host and News Editor for the Bisrat Sport radio show, and worked as a football analyst with Kuas Meda. He co-created the Rigore sports show. He was also sports and political stringer for Voice of America’s Horn of Africa Service. His articles were selected among the Top 10 in Africa by the AIPS Sport Media Awards in 2018 and 2022.

Related Posts

Diribe Welteji banned for two years

The Court of Arbitration for Sport (CAS) has partially upheld an appeal by World Athletics against the Ethiopian National Anti-Doping Office (ETH-NADO) and middle-distance runner Diribe Welteji Kejelcha (Ethiopia). Ms…

ጆን ቴሪ በቼልሲ ጊዜያዊ አሰልጣኝነት ምርጫ ማዘኑን ገልጿል

የቀድሞው የቼልሲ የመሀል ተከላካይ ጆን ቴሪ ጥር ላይ በተሰናበቱት አሰልጣኝ ኤንዞ ማሬስካ ምትክ የጊዜያዊ አሰልጣኝነት እድል ባለማግኘቱ ደስተኛ እንዳልሆነ ገልጿል፡፡  ጆን ቴሪ በቼልሲ አካዳሚ በበጎ ፈቃድ አሰልጣኝነት በወር ሁለት ቀን…

Leave a Reply

You Missed

Ethiopia Bunna appoints new chairman 

Ethiopia Bunna appoints new chairman 

Diribe Welteji banned for two years

Diribe Welteji banned for two years

ጆን ቴሪ በቼልሲ ጊዜያዊ አሰልጣኝነት ምርጫ ማዘኑን ገልጿል

ጆን ቴሪ በቼልሲ ጊዜያዊ አሰልጣኝነት ምርጫ ማዘኑን ገልጿል

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አዲስ አሰልጣኝ አግኝቷል

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አዲስ አሰልጣኝ አግኝቷል

ከራባት እስከ አጋዲር፡ AFCON 2025ን የሚያስተናግዱ ዘጠኝ ስታዲየሞች

ከራባት እስከ አጋዲር፡ AFCON 2025ን የሚያስተናግዱ ዘጠኝ ስታዲየሞች

የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ዳሰሳ

የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ዳሰሳ